Micah 3

መሪዎችና ነቢያት ተገሠጹ

1ከዚያም እኔ እንዲህ አልሁ፤

“እናንት የያዕቆብ መሪዎች፤
እናንት የእስራኤል ቤት ገዦች ስሙ፤
ፍትሕን ማወቅ አይገባችሁምን?
2መልካሙን ጠላችሁ፤ ክፉውንም ወደዳችሁ፤
የሕዝቤን ቈዳ ገፈፋችሁ፤
ሥጋቸውንም ከዐጥንቶቻቸው ለያችሁ፤
3የሕዝቤን ሥጋ በላችሁ፤
ቈዳቸውን ገፈፋችሁ፤
ዐጥንቶቻቸውንም ሰባበራችሁ፤
በመጥበሻ እንደሚጠበስ፣
በድስት እንደሚቀቀል ሥጋ ቈራረጣችኋቸው።”

4እነርሱም ወደ እግዚአብሔር ይጮኻሉ፤
እርሱ ግን አይመልስላቸውም፤
ካደረጉት ክፋት የተነሣ፣
በዚያ ጊዜ ፊቱን ከእነርሱ ይሰውራል።
5 እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤

“ሕዝቤን የሚያስቱ ነቢያት፣
ሰው ሲያበላቸው፣ ‘ሰላም አለ’ ይላሉ፤
ሳያበላቸው ሲቀር ግን፣
ጦርነት ሊያውጁበት ይነሣሉ።
6ስለዚህ ሌሊቱ ያለ ራእይ፣
ጨለማውም ያለ ንግርት ይመጣባችኋል፤
በነቢያት ላይ ፀሓይ ትጠልቅባቸዋለች፤
ቀኑም ይጨልምባቸዋል።
7ባለ ራእዮች ያፍራሉ፤
ንግርተኞችም ይዋረዳሉ፤
ሁሉም ፊታቸውን ይሸፍናሉ፤
ከእግዚአብሔር መልስ የለምና።”
8እኔ ግን፣
ለያዕቆብ በደሉን፣
ለእስራኤልም ኀጢአቱን እነግር ዘንድ፣
ኀይልን በእግዚአብሔር መንፈስ፣
ፍትሕና ብርታትም ተሞልቻለሁ።

9እናንተ የያዕቆብ ቤት መሪዎች፣
እናንት የእስራኤል ቤት ገዦች፣
ፍትሕን የምትንቁ፣
ትክክለኛ የሆነውንም ነገር ሁሉ የምታጣምሙ፤ ስሙ፤
10ጽዮንን ደም በማፍሰስ፣
ኢየሩሳሌምን በክፋት የምትገነቡ፤ ስሙ።
11መሪዎቿ በጕቦ ይፈርዳሉ፤
ካህናቷ ለዋጋ ሲሉ ያስተምራሉ፤
ነቢያቷም ለገንዘብ ሲሉ ይናገራሉ።
ነገር ግን በእግዚአብሔር ላይ ተደግፈውም፣
እግዚአብሔር በመካከላችን አይደለምን?
ምንም ዐይነት ክፉ ነገር አይደርስብንም” ይላሉ።
12ስለዚህ በእናንተ ምክንያት፣
ጽዮን እንደ ዕርሻ ትታረሳለች፣
ኢየሩሳሌም የፍርስራሽ ክምር ትሆናለች፤
የቤተ መቅደሱም ኰረብታ ዐረም የበቀለበት ጕብታ ይሆናል።
Copyright information for AmhNASV